ኢሕአዴግ ክርስትያኖችን የሚያስፈራራበት ምናባዊ ጭራቅ፡ ‹‹ወሐቢያ››
ለዛሬ ልጽፍ የፈለግኩት ስለወቅታዊው የሙስሊሞች የመብት ጥያቄ ሲሆን የኢሕአዴግ መንግሥት (በተለይ ደግሞ ፌዴራል ጉዳዮች) በክርስትያን ወንድምና እኅቶቻችን አዕምሮ ውስጥ ከሙስሊሞች ጋር አያይዞ እየፈጠረው ያለውን ሥጋት መሠረት አልባነት ለማሳየትም እሞክራለሁ። የሙሉውን ጽሑፌን መንፈስና ሙግት ሊጠቀልልልኝ በሚችል አንድ ዐረፍተ ነገር ብጀምር ደስ ይለኛል፡ –‹‹እኛ ኢትዮጵያውያን ሙስሊሞች ለክርስትያን ኢትዮጵያውያንም ሆነ የጋራችን ለሆነው ሕገ-መንግሥታዊ የሃይማኖት ነጻነት በፍጹም ሥጋትአይደለንም! ‹አበበ በሶ በላ ወይ?››ተብሎ ሲጠየቅ ‹‹ሉሌ ካባ ለበሰ››ብሎ መመለስ ስህተት ነው! መንግሥት የተጠየቀው ቀጥተኛ የመብት ጥያቄ ሆኖ ሳለ ‹‹ኢስላማዊ መንግሥት ሊያቋቁሙ ያሰቡ አሉ››ብሎ መመለስ በምን ዓይነት አመክንዮ ነው ልክ ሊሆን የሚችለው? አወሊያ ተሰብስቦ ሰሚ ያጣ ጩኸቱን ሲያሰማ የነበረው በመቶ ሺዎች የሚቆጠር ሕዝብ መቼ ነው ኢስላማዊ -

መንግሥት እንዲቋቋምለት የጠየቀው? ‹‹ኢስላማዊ መንግሥት ይቋቋም››ያሉ ሕልመኞች ካሉስ (አሉ ወይ የሚለውን በኋላ አነሣዋለሁ) እነሱ ለብቻ ይጠየቁ እንጂ ሕዝበ ሙስሊሙ ምን አገባው? በቁም ነገር መሐል ይህን ዓይነት ቀልድ መደባለቅ እንዴት ተገቢ ሊሆን ቻለ? …ሁለት ዓላማዎችን ያዘለ መሆኑ ግልጽ ነው። አንደኛው ዓላማ መብት ጠያቂዎቹን ራሳቸውን ማስፈራራት ነው። ጥያቄያቸውን አጣምሞ በማቅረብ እና ያልተገባ ትርጉም በመስጠት እንዲደነግጡና እንዲሸማቀቁ፣ ሕዝበ ሙስሊሙና ኮሚቴዎቹ ‹‹ኧረ እኒህ ሰዎች አመረሩብን!››በሚል ፍርሐት ተወጥረው ጥያቄያቸውን እንዲተዉት ነው። ሁለተኛው ዓላማ ደግሞ የሌላ ሃይማኖት ተከታይ የሆኑ ኢትዮጵያውያን (በዋነኝነት ሕዝበ ክርስትያኑ) የሸሪዓ መንግሥት የማቋቋም ዓላማ (ሕልም ብለው ይቀላል) ያለን መስሏቸው እንዲደነግጡና ከጎናቸው እንዲቆሙ ለማድረግ ነው። እየተነዛ ያለውን ፕሮፓጋንዳ ሐሰትነት ማሳየት ደግሞ ከባድ አይደለም። እውነታዎቹን በዚህ ጽሑፍ አብረን እናያቸዋለንና። እስቲ ከመሠረቱ ለመጀመር ይህ ኢስላማዊ መንግሥት ለማቋቋም በመንቀሳቀስ እየታማ ያለው ምናባዊ ጭራቅ “scapegoat”(ወሐቢያ) ምን እንደሆነ ለማየት እንሞክር።
‹‹ወሐቢያ››ምንድነው?
‹‹ወሐቢያ››ባሁኑ ሰዓት እጅግ ተለጥጦ የመጅሊስ ተቃዋሚዎች የወል ሥም ሊሆን ምንም ያህል አልቀረውም። እኛ ግን መጀመሪያ ትክክለኛ ትርጉሙን እንየው።
‹‹ወሐቢያ››ሥሙ ራሱ የተወሰደው ‹‹ሙሐመድ ኢብን ዐብዱልወሐብ››ከተባሉ የኢስላም ምሁር ሲሆን ሸኹ ከሁለት መቶ ዓመታት በፊት ዐረቢያ ውስጥ ኢስላማዊ አምልኮዎችን ከባሕል ተጽእኖ ለማላቀቅ የታገሉ መሆናቸው ይነገርላቸዋል። ይከተሉት የነበረው የአስተሳሰብ መስመር ዋነኛ አነቃቂ የነበሩ በመሆናቸው ሥማቸው የበለጠ ገኖ ሊወጣ ችሏል። በሂደት በሙስሊሙ ማኅበረሰብ ውስጥ የእኒህን ሸኽ ሃይማኖታዊ የአስተሳሰብ መስመር የሚከተሉ ሙስሊሞች ‹‹ወሐቢያ››በሚል መጠራት ጀመሩ። ይህ ሥያሜ ደግሞ በነገራችን ላይ ተለምዷዊ እንጂ መደበኛ ሥም አይደለም። እነሱም ራሳቸውን የሚጠሩት ሙስሊሞች እንጂ ‹‹ወሐቢያ››በሚል አይደለም። ልክ መንፈስን በማጥራት ላይ ያተኩር የነበረው አስተሳሰብ ተከታዮች ‹‹ሱፊያ››ተብለው ይጠሩ እንደነበረው ሁሉ ‹‹ወሐቢያ›ም በተለምዶ የሚታወቀው በአምልኳዊ የአስተሳሰብ መስመርነቱ እንጂ በፖለቲካዊ እንቅስቃሴነቱ አይደለም። ተጽእኖውም በሙስሊሙ ኅብረተሰብ አምልኳዊ አፈጻጸም ላይ የተወሰነ ሆኖ ነው የምናገኘው። ይኸው የአስተሳሰብ መስመር ታዲያ የሚታወቅባቸው አመለካከቶች (ፈትዋዎች) ነበሩት፤ አሉትም። ለምሳሌ ነቢዩ ሙሐመድ የተወለዱበትን ቀን እንደበዓል አድርጎ ማክበር ትክክል እንዳልሆነ ያምናሉ፤ ያስተምራሉ። ጺም ማሳደግና ሱሪን ማሳጠር ተገቢ እንደሆነም ያስተምራሉ። ሌሎችም አመለካከቶች አሏቸው።ባጭሩ ምንም እንኳ ሥያሜውን የሚቀበሉም ሆነ ራሳቸውን ‹‹ወሐቢያ››በሚል የሚገልጹ ሙስሊሞች ባይኖሩም በተለምዶ ‹‹ወሐቢያ››ተብለው የሚጠሩት ከላይ የጠቀስናቸውን ኢስላምንና ሙስሊሞችን ብቻና ብቻ የተመለከቱ አመለካከቶችን የሚያቀነቅኑ ሙስሊሞችን ነበር። ዛሬ ግን አዘውትረው በእምነታችን ጣልቃ እየገቡ ለያዥ ለገራዥ ያስቸገሩን የተከበሩ ሚኒስትር ዶክተር ሽፈራው መጥተው ‹‹አይ! ወሐቢያ ማለት ኢስላማዊ መንግሥት ለማቋቋም እንቅስቃሴ የሚያደርግ ቡድን ነው!››እያሉን ይገኛሉ። እንዴት ነው ነገሩ…እርስዎ ከኛ በላይ ስለሃይማኖታችን ያውቁ ይሆን እንዴ የተከበሩ ሚኒስትር?
እስቲ የተወሰኑ ጥያቄዎችን አንሥቼ ራሴ እየመለስኳቸው ልሂድ…ለመሆኑ ‹‹ወሐቢያ››የሚባል በመደበኛ መልኩ የተዋቀረ ድርጅት በአገራችን አለ እንዴ?
እኔው ልመልሰው። ‹‹ወሐቢያ››የሚባል ተቋም ከነጭራሹ በአገራችን የለም። ‹‹ወሐቢያ››ኢስላማዊ የአስተሳሰብ መስመር እንጂ ቡድን አይደለም። አስተሳሰቡም ኢስላም ላይ ብቻና ብቻ የተወሰነ ነው –መንግሥትን የሚመለከት አይደለም። አንድ ሙስሊም ደግሞ የፈለገውን የአስተሳሰብ መስመር መርጦ መከተል ይችላል –በዚህ መንግሥት ሊረበሽ አይገባውም። ጋዜጠኛ ሑሴን ኸድር ሰሞኑን በዕንቁ መጽሔት ‹‹ነፋስን በወጥመድ››በሚል ርእስ ያወጣው ጽሑፍ ወሐቢያ የሚባል ተቋምም ሆነ ቡድን አለመኖሩን በመጥቀስ መንግሥት በ‹‹ወሐቢያ››ላይ የጀመረው ዘመቻ ንፋስን በወጥመድ ለመያዝ ከመሞከር ያልቀለለ መሆኑን አሳይቶ ነበር። በምክንያነት የጠቀሰውም ‹‹ወሐቢያ››አስተሳሰብ እንጂ ቡድን አለመሆኑን ነበር።
እኔው ልመልሰው። ‹‹ወሐቢያ››የሚባል ተቋም ከነጭራሹ በአገራችን የለም። ‹‹ወሐቢያ››ኢስላማዊ የአስተሳሰብ መስመር እንጂ ቡድን አይደለም። አስተሳሰቡም ኢስላም ላይ ብቻና ብቻ የተወሰነ ነው –መንግሥትን የሚመለከት አይደለም። አንድ ሙስሊም ደግሞ የፈለገውን የአስተሳሰብ መስመር መርጦ መከተል ይችላል –በዚህ መንግሥት ሊረበሽ አይገባውም። ጋዜጠኛ ሑሴን ኸድር ሰሞኑን በዕንቁ መጽሔት ‹‹ነፋስን በወጥመድ››በሚል ርእስ ያወጣው ጽሑፍ ወሐቢያ የሚባል ተቋምም ሆነ ቡድን አለመኖሩን በመጥቀስ መንግሥት በ‹‹ወሐቢያ››ላይ የጀመረው ዘመቻ ንፋስን በወጥመድ ለመያዝ ከመሞከር ያልቀለለ መሆኑን አሳይቶ ነበር። በምክንያነት የጠቀሰውም ‹‹ወሐቢያ››አስተሳሰብ እንጂ ቡድን አለመሆኑን ነበር።
ሌላ ሊረሳ የማይገባው ነገር ደግሞ ኢትዮጵያዊው ሙስሊም ከዓለማቀፉ ኢስላማዊ እንቅስቃሴም ሆነ የግጭት ክስተቶች የሚለይበት በርካታ ነጥብ እንዳለ ነው። ይህን አስመልክቶ ሰፊ ጥናት ያደረጉ የውጭ ምሁራኖች በሽ ናቸው። እዚሁ ቅርብ ሆኖ፣ በሩቁ ሳይሆን አብሮ ከሙስሊሙ ጋር ኖሮ ለዓመታት በርካታ ጥናቶችን ያጠናው ኖርዌያዊው ዶክተር ቴሪ አስቴቦ ከመሰል ምሁራን አንዱ ነው፡ ፡ የእሱን ጥናት ወረቀቶች እና ድምዳሜዎች ማየቱ ብቻውን በሥም መመሳሰል ከመሸወድና በሌላው ዓለም ያሉ ክስተቶችን ኢትዮጵያውያን ሙስሊሞች ላይ በሐሰት ከመደፍደፍ ያድናል፡፡
ሃይማኖታዊ ግጭቶችን ከእንቅስቃሴ ጋርየማደባለቅ አባዜ
የሕዝበ ሙስሊሙን የልብ ትርታ ከማዳመጥ እጅግ የራቁ አንዳንድ የኢሕአዴግ ባለሥልጣናት ይህንኑ ‹‹ኢስላማዊ መንግሥት ሊያቋቁም የሚፈልግ ቡድን አለ››የሚል ባዶ ክርክራቸውን ለሌሎች ለማሳመን ከሚያቀርቡት መረጃ አንዱ ካሁን ቀደም የተከሰቱ የሃይማኖት ግጭቶችን ደጋግሞ ማንሣት ነው። ኢትዮጵያውያን ሙስሊሞችና ክርስትያኖች በሕዝብ ደረጃ በጥሩ መቻቻል ታሪካችንን አሳልፈናል። ሃይማኖታዊ ጭቆና ሲያደርሱ የነበሩትም መሪዎች እንጂ ሕዝቡ እርስ በርስ በመተሳሰብ ነው ለዘመናት የኖረው። ይሁንና ይህ ማለት ግን የሃይማኖት ግጭቶች እዚህና እዚያ አልተከሰቱም ማለት አይደለም። በሁሉም ሃይማኖት ውስጥ እጅግ ጥቂት ጽንፈኞች መኖራቸውና ግጭት ፈጥረው ማወቃቸው ግልጽ ነው። በዚህ ሁላችንም ብናዝንም እኒህ ግጭቶች ግን የአብሮነት ሕይወታችንን ያደበዘዙ አልነበሩም። የዘመነኛው የአብሮነት ታሪካችን ዋነኛ አካልም አይደሉም። ይልቁንም በኩንታል ስንዴ መሐል የተገኙ ጥቂት እንክርዳዶች ናቸው፤ አልያም በኩንታል ጤፍ መሐል የተሰነቀሩ ጥቂት ጉድፎች!
በነዚህ ግጭቶች ያላዘነ ማንም የለም። ጅማ ውስጥ የነበሩት ግጭቶች የሁላችንንም ልብ አድምተዋል። እኔ በግሌ ሙስሊም ብሆንም አንድ ቤተ ክርስትያን ሲቃጠል በጣም እበሳጫለሁ፤ ጓደኞቼም ቢሆኑ ያዝናሉ። ማንም ጥቂት እንኳ የአማኝ መልካምነት በልቡ ያለው ክርስትያንም ሆነ ሙስሊም በዚህ መሰል ድርጊቶች ማዘኑ አያጠራጥርም። እኔ ለምሳሌ በርካታ ክርስትያን ጓደኞች አሉኝ። ሁሉም ግን ሙስሊም ባይሆኑም ጉራጌ ዞን ውስጥ በተቃጠሉት መስጊዶች አዝነዋል፤ ቅዱስ ቁርኣን በአንዳንድ አካባቢዎች ለመጸዳጃነት በመዋሉም ተከፍተዋል። ልክ እንደክርስትያን ወንድሞቹ እና እኅቶቹ ሁሉ ሕዝበ ሙስሊሙም ክርስትያኖች ላይ በአንዳንድ ጽንፈኞች የተፈጸሙ አስከፊ ድርጊቶች ይረብሹታል፤ ያሳዝኑታል። እስካሁን በጽንፈኞች በተቃጠሉ አብያተ ክርስትያናትም በጣም አዝኗል።
ጥንታዊው ዋልድባ ገዳምን በተመለከተም ሆነ የዝቋላ ደን ቃጠሎ ለቤተ ክርስትያኑ ደህንነት አስጊ መሆኑ የክርስትያኖች ብቻ ሳይሆን የኛም ችግርና ሥጋት ነው። በአሕባሽ ምክንያት እየተፈጠረብን ያለው ዘርፈ ብዙ አገራዊ ችግርም ቢሆን ለሕዝበ ክርስትያኑም ጭምር አሳሳቢ ጉዳይ መሆኑን ከተወያየኋቸው ክርስትያን ሰባኪያንም ሆነ ከጓደኞቼ ብዙ ሰምቻለሁ። ይህ ከሞላ ጎደል የአብሮነታችን እውነታ፣ ማንም ጨካኝ ንጉሥ እንኳ ከልባችን ሊፍቀው ያልቻለው የእርስ በርስ መተዛዘናችን ውጤት እንደሆነ ይሰማኛል።
ለነዚህ ጥቂት ግጭቶች በተለየ ተጠያቂ የማደርገው ሃይማኖት አይኖርም፤ በሁላችንም መሐል እጅግ ጥቂት ጽንፈኞች መኖራቸውን እረዳለሁና። የኔ ሙግት ‹‹እነዚህ ጥቂት ግጭቶች ጽንፈኞች በሚያደርጓቸው የሃይማኖት ትንኮሳዎች ምክንያትነት የሚፈጠሩ ናቸው እንጂ የእንቅስቃሴ ውጤቶች አይደሉም››የሚል ነው። ለምሳሌ አንድ ቦታ ላይ አንድ ጽንፈኛ ሰው በሌላ ሃይማኖት ተከታዮች ላይ የሆነ ግላዊ ጥቃት ወይም ትንኮሳ ቢሰነዝር፣ እነሱ ደግሞ ተናድደው የሆነ ሌላ ጽንፈኛ እርምጃ ቢወስዱ ‹‹ግጭት ተፈጠረ››እንላለን እንጂ ግጭቱን እንቅስቃሴ ወለድ አናደርገውም።
በነገራችን ላይ በሃይማኖት ግጭት ውስጥ የተሳተፈ ሁሉ ‹‹ጽንፈኛ ነው››የሚል ድምዳሜ እየሰጠሁ አይደለም። ግጭት ‹‹ሃይማኖቴ ተነክቷል››ብሎ ባሰበ፣ ተነክቶበት በተቆጣም ሆነ በተሳሳተ መረጃ (false alarm) ምክንያት በንጹሐን ሰዎች ሊፈጸም ይችላል። ስለዚህ በጥቅል ሁሉንም በ‹‹ጽንፈኝነት››ቅርጫት ውስጥ እየከተትኩ አይደለም።
ከላይ የጠቀስኳቸው የመንግሥት ባለሥልጣናት ግን እኒህን ግጭቶች በማውሳት ‹‹ኢስላማዊ መንግሥት የማቋቋም ዓላማ ያላቸው ሰዎች አሉ››የሚለውን ንግግራቸውን ሊግቱን ይሞክራሉ። ይህ ከባድ ስህተት ነው። ሃይማኖታዊ ግጭት ሌላ…ኢስላማዊ መንግሥት መመሥረት ሌላ! ምን አገናኛቸው? ለምንስ ነው አላስፈላጊና ባዶ ሥጋቶችን በሕዝቡ ላይ በመጫን እርስ በርስ በዐይነ ቁራኛ የሚተያይ ትውልድ ለመፍጠር የሚጥሩት? የሕዝብ በዘርና በሃይማኖት የጎሪጥ መተያየት ለማንም አይጠቅምምኮ!
በጣም የሚገርመው ነገር ፌዴራል ጉዳዮች በተደጋጋሚ ለጋዜጠኞች እና ለሕዝብ ግንኙነት ሠራተኞች በሰጠውና እኔም ራሴ በተገኘሁበት ሥልጠና ‹‹የሃይማኖት ግጭቶችን ስትዘግቡ ግጭቱን በማያባብስ መልኩ መሆን አለበት። ማጋነን እና መደጋገም አያስፈልግም››እያሉ ደጋግመው አስተምረውን ነበር። የተከበሩ ዶክተር ሽፈራው ራሳቸው ይህንኑ አጽንኦት ሰጥተው ደጋግመው ነግረውናል። ዛሬ ግን ራሳቸው በተመሣሣይ ስህተት ላይ ሲወድቁ እያየናቸው ይመስላል። ሕዝበ ሙስሊሙ ያነሣውን የመብት ጥያቄ ለማድበስበስ በሚመስል አኳኋን ‹‹ወሐቢያ የሚባል ቡድን እስላማዊ መንግሥት ሊመሠርት ተነስቷል!››እያሉ ክርስትያን ወንድሞቻችንን እያስበረገጉ ነው።
ሚኒስትሩ ይህንን ያሉት ለብቻ በሌላ ጉዳይ
ላይ ቢሆን ቢያንስ ‹‹ስለማናውቃቸው ሌሎች ቡድኖች እያወሩ ነው››እንል ነበር። እሳቸው ግን ይህንኑ እያሉ ያሉት ስለሕዝበ ሙስሊሙ የመብት ጥያቄ ሲጠየቁ በመሆኑ ‹‹ወሐቢያ››በሚል የምናባዊ ጭራቅ ሥያሜ ጥቃት እየሰነዘሩ ያሉት ሙስሊሙ ላይ ነው ማለት ነው። ይህ ደግሞ ተገቢ አይደለም።
እኛ ሙስሊም ኢትዮጵያውያን የሸሪዓ መንግሥት እንደማንፈልግ ሦስት ተጨባጭ ምክንያቶችን እንደሚከተለው እጠቅሳለሁ፡-
1. ዓለማዊው ሕገ-መንግሥታችን በቂያችን ነው!
በ 1987 የጸደቀው ሕገ-መንግሥት በውስጡ ያዘላቸው ሃይማኖትን የተመለከቱ አንቀጾች የሕዝበ ሙስሊሙን ሃይማኖታዊ ፍላጎት ለማሟላት እጅግ በቂ ናቸው! በዋነኝነት የሃይማኖትና መንግሥት መለያየት፣ የአንዱ ባንዱ ጣልቃ አለመግባት እና የመንግሥታዊ ሃይማኖት አለመኖር እጅግ መሠረታዊና በሙሉ ልብ የምንቀበላቸው ወርቃማ አናቅጽት ናቸው። በተጨማሪም አንድ ሰው የፈለገውን ሃይማኖት ያለማንም አስገዳጅነት መምረጥ፣ መስበክ፣ ማስፋፋት፣ እንዲሁም ከመሰሎቹ ጋር ተባብሮ ተቋም የመመሥረት መብት እንዳለው ይኸው ሕገ-መንግሥታችን አስቀምጦታል። እኒህን ሕገ-መንግሥታዊ መብቶችና ነጻነቶች ልክ እንደሌላው ኢትዮጵያዊ ሁሉ በሙሉ ልባችን እንቀበላቸዋለን። የትኛውም ሙስሊም ቢጠየቅ ከዚህ ውጭ ፍላጎትም ዓላማም የለውም። የሌሎችን የማመን መብት ለመጋፋትም የሚፈልግበት ምክንያታዊ መነሻ የለውም።
ሕዝበ ሙስሊሙም ቢሆን ያነሣው ጥያቄ ‹‹አሕባሽ የተባለው ቡድን መጥቶ ይህን ሕገ-መንግሥታዊ መብታችንን እየነፈገን ነው! አንድ በሉልን! በሃይማኖታችን ጉዳይ ጣልቃ አትግቡብን! የተቋም መሪዎቻችንን እራሳችን እንድንመርጥ ዕድል ስጡን!››የሚል እንጂ የኢስላማዊ መንግሥት ጥያቄ አይደለም። ይህ ሙስሊሙም ክርስትያኑም፣ ቡድሂስቱም ሂንዱዪስቱም አንድ ላይ በሚኖርባቸው አገራት ሁሉ በተጨባጭ የሚታይ እውነታ ነው። በሙስሊሙ ዓለም እንደ ተምሳሌት የሚቆጠሩ አንድ እውቅ ዶክተር ይህንኑ አስመልክተው ሕንድ ውስጥ ያለውን ሁኔታ ሲናገሩ የሚከተለውን ተናግረው ነበር፡ –‹‹በእስልምና ግዴታ የተደረገብኝን ነገር ከመፈጸም የሚከለክለኝም ሆነ በእስልምና ክልክል የሆነን ተግባር እንድፈጽም የሚያስገድደኝ ዓለማዊ ሕግ እስካሁን ሕንድ ውስጥ የለም። ስለዚህ በሕንዳዊነቴ እኮራለሁ!››ነበር ያሉት።
2. ሸሪዓ ኢትዮጵያ ውስጥ ለማቋቋም ማሰብ አዋጭአይደለም!
እንደው ከተራ ሥሌት አንጻር እንኳ ብናስበው ሸሪዓን ኢትዮጵያ ውስጥ ማቋቋም በፍጹም አዋጭ አይደለም። ምክንያቱም ኢትዮጵያ ሕብረ ብሔራዊ እና ሕብረ ሃይማኖታዊ አገር ናት። የተለያዩ እምነት ተከታዮች በከፍተኛ ቁጥር በሚገኝበት አገር ውስጥ ሸሪዓ እንዴት አዋጭ ሆኖ ሊታሰብ ይችላል? እዚህች አገራችን ውስጥኮ ቢያንስ 40 ሚሊዮን ክርስትያኖች አሉ። ይህን ያህል ቁጥር ያለው ክርስትያን ባለበት አገር ውስጥ ሸሪዓ የማቋቋም አጀንዳ ይዞ አንድ ቡድን እንዴት ሊነሣ ይችላል? ሥሌቱ በፍጹም ልክ አይመጣም!
የአገሪቱ ግማሽ ሕዝብ የማያምንበት የእምነት መጽሐፍ በየትኛው ኃይል ነው መተዳደሪያ ሊሆን የሚችለው? እንዲህ ዓይነት የማይሳካ ሕልም ሰንቆ የሚንቀሳቀስ ኢስላማዊ ቡድን ኢትዮጵያ ውስጥ በፍጹም የለም! ሊኖርም አይችልም። ቢኖርም ከማንም በፊት ፊት የሚነሣው ሕዝበ ሙስሊሙ ራሱ ነው። ከእልቂት ያለፈ በተጨባጭ ሊፈጥረው የሚችለው ውጤትም የለም!
ሙሉ በሙሉ ሙስሊም ባለባቸው አገራት ውስጥ ሸሪዓ ማቋቋም የራሱ ትርጉምም ሆነ አስፈላጊነት ሊኖረው ይችላል። ያ የአገሪቱ ሕዝብ በራሱ ምርጫ የሚወስነው ጉዳይ ነው። ሌላው ቀርቶ ሙሉ በሙሉ ሙስሊም ሆነው እንኳን ሸሪዓ ያልተቋቋመባቸው ምን ያህል አገራት እንዳሉ ብናስበው ቁጥሩ የትዬለሌ ነው። ከነጭራሹ የሸሪዓ አስተዳደር ያለባቸው አገራት ቁጥር ከአንድ እጅ ጣት አይበልጥም። ታዲያ ከዚህ በላይ ያልተጨበጠ ሥጋት ከየት መጥቶ ነው ኢትዮጵያ ውስጥ ሸሪዓን ለማቋቋም የሚንቀሳቀስ ቡድን አለ በሚል በገደምዳሜ ወደ ሕዝበ ሙስሊሙ የመብት ጥያቄ ጣት የሚቀሰረው? ሕዝበ ሙስሊሙን በጅምላ እና ተከሳሹን አካል ለይቶ ባላወጣ መልኩ መፈረጅ ክርስትያኖችን በውሸት ሥጋት ለማስደንገጥ ካልሆነስ እንዴት ሊጠቅም ይችላል?
3. ጥያቄዎቻችን ከመሠረታዊነት ዘለው አያውቁም!
እኛ ሙስሊሞች እንደ ሕዝብ ስናነሣቸው የነበሩት የመብት ጥያቄዎች ከመሠረታዊነት ዘለው አያውቁም። በኢሕአዴግም ዘመን ቢሆን በተለይ ላለፉት አምስት ዓመታት ስንጠይቃቸው የነበሩ ጥያቄዎች ከሕግ አንጻር እጅግ ትናንሽ ነበሩ፤ ናቸውም። ‹‹ሴቶቻችን በትምህርት ቤት ሂጃብ አይከልከሉ፤ ወንዶቻችን ትምህርት ቤት ውስጥ ሶላት መስገድ አይከልከሉብን፤ እምነታችን የማንነታችን አካል ነውና እንደጃኬት አውልቀነው ልንገባ አንችልም፤ ሕገ-መንግሥቱ የደነገገውን መብት የትምህርት ተቋማት ዲኖችና ዳይሬክተሮች አይከልክሉን!››ከማለት ያለፈ ጥያቄ አላነሣንም። ‹‹አሜሪካን በመሳሰሉ የሴኪውላሪዝም ተምሳሌት አገራት እንኳ የሚፈቀዱ ተግባራትን አንከልከል››ከማለት ውጭ ምንም አላልንም። ነው ወይስ የኢትዮጵያው ሴኪውላሪዝም ከአሜሪካው እንኳ ተሸሎ ተገኘ?
ተቋማችንን መጅሊስም ቢሆን ‹‹በመረጥናቸው ሰዎች ይተዳደር››ከማለት የዘለለ ምንም አላልንም። ይህ ደግሞ ‹‹በዴሞክራሲ አስተዳድራለሁ››ለሚል መንግሥት እጅግ ቀላልና ቀጥተኛ ጥያቄ ነው፤ ውስብስብ አይደለም። እንኳንስ የእምነት ተቋምና መንግሥትም ቢሆን በሕዝቡ መመረጥ አለበት ተብሎ አይደል ምርጫ የሚባል ነገር ያስፈለገው?
ከአመክንዮአዊ አስተሳሰብ እናፈንግጥ ካላልን በስተቀር እኒህን የመሳሰሉ መሠረታዊ መብቶቹ እንዲጠበቁለት የሚታገል ሰው ሸሪዓ ለማቋቋም ሊያስብ አይችልም! በጭራሽ! አንድ ጠኔ ያጠማረረውና በረሐብ ሊሞት የደረሰ ሰው ‹‹ምግብ ስጡኝ››ብሎ ሊጠይቅ ይችል ይሆናል እንጂ ‹‹ዶሮ ወጥ ካልሰጣችሁኝ አንቄ እገላችኋለሁ!››ብሎ ሊያስፈራራ ይችላል ብሎ ማሰብ ከምክንያታዊነት ጋር እጅጉን ይጣረሳል። በተመሳሳይ ሁኔታ አንዲት ‹‹ሻሼን ሳላወልቅ እንድማር ፍቀዱልኝ!››እያለች የምትማጠን ምስኪን እኅታችንን ‹‹ሸሪዓን ለማቋቋም እያሰበች ነው››ብሎ መክሰስ፣ አንድ ‹‹ከሊባኖስ ያመጣችሁትን ሃይማኖት አልፈልግምና ባካችሁ ሰላም ስጡኝ!››እያለ የሚማጠን ምስኪን ወንድማችንን ‹‹ሸሪዓን ለማቋቋም ዶልተሃል››በሚል መወንጀል ከእውነታው ሃዲድ የሚያስፈነግጥ አቋም ነው። ይህንን የምለው ባለሥልጣናቱ ስለሸሪዓ የማቋቋም እንቅስቃሴ ሲያወሩ እየጠቆሙ ያሉት ወደእነዚህ የመብት ጥያቄዎች ስለሆነ ነው! በእውነቱ በጣም ተሳስተዋል! ኢስላማዊ መንግሥት ይቅርና ትዳር ነክ ጉዳዮቻችንን ለፈለገ ሰው ለማስተናበር የተቋቋመው ሸሪዓ ፍርድ ቤታችን እንኳ በፈርጀ ብዙ ችግሮች የተጠፈረ ተቋም ነው። እሱን እንኳ ለማስተካከል አቅም የሌላቸው ሰዎች ‹‹ሸሪዓ ሊያቋቋሙ ያስባሉ››ብሎ መጠርጠር እንኳ የማይታለምና የማያስኬድ ነው።
መንግሥትን በካራቴ?!
ፌዴራል ጉዳዮች በቅርቡ ባዘጋጀው የጋዜጠኞች ሥልጠና ላይ ሕዝበ ሙስሊሙን በጭራሽ ያላገናዘበ ለብ ለብ ወረቀት ያቀረቡ አንዲት ወይዘሮ ‹‹ሙስሊም ካራቴ አሠልጣኞች በዝተዋል››የሚል አስገራሚ እውነታ ከጠቀሱ በኋላ ይህንኑም ከዚሁ ‹‹ኢስላማዊ መንግሥት የማቋቋም አባዜ››ጋር አያይዘውታል። ‹‹የባሰው መጣ››ይሏል ይሄ ነው! እንዴት ዓይነት ጉደኛ ድምዳሜ ነው ይሄ? ‹‹ሙስሊም ካራቴ አሠልጣኞች በዝተዋል አልበዙም››የሚለውን ማረጋገጡ ሌላ ጥናት የሚፈልግ ነገር ሆኖ ‹‹እንዲህ ዓይነት ድምዳሜ እንዴት ሊወስዱ ቻሉ?››ብለን ብንጠይቅ መልሱ ‹‹ክርስትያኖችን ከማስፈራራት ውጭ ሊሆን አይችልም››ነው።
አንድ ቀላል ጥያቄ ለወይዘሮዋ ብንጠይቃቸው ሥጋታቸው ባዶ መሆኑን እንረዳለን…ለመሆኑ መንግሥት የሚቋቋመው በካራቴና በጫማ ጥፊ ነው እንዴ? ኢሕአዴግ ጦረኛውን ደርግ ደምስሶ የገባው ካራቴ ስለሠለጠነ ነበር እንዴ? ለምን የማይመስል ማስፈራሪያ እየፈጠራችሁ ክርስትያን ወንድሞቻችንን ታስበረግጋላችሁ? ለምን በአሉባልታ ታቃቅሩናላችሁ? ለምንስ ትከፋፍሉናላችሁ?
አንድ መንግሥት ለመገልበጥና የራሱን መንግሥት ለማቋቋም የሚፈልግ ቡድንኮ ከተማ ውስጥ ካራቴ ከመሠልጠን ይልቅ ጫካ ነው የሚገባው! በሊማሊሞ ነው የሚያቋርጠው! ታዲያ የትኛው ጫካ ውስጥ ታጥቀን ገብተን ነው እንዲህ ዓይነት ሐሜት የሚነዛብን?
የትኛውም ሃይማኖት ቢሆን ስገምት ለስፖርታዊ እንቅስቃሴና ለአካል ብቃት ጥሩ ዕይታ ይኖረዋል። እስልምናም ከዚህ የተለየ ሊሆን አይችልም። ሙስሊም ካራቴ አሠልጣኞች በዝተውም ከሆነ ለምን ከኢስላማዊ መንግሥት የማቋቋም ተረት ጋር እንዳያያዛችሁት ለኔ ግራ ነው። በአንድ ሙያ ላይ የአንድ ሃይማኖት ተከታዮች በዛ ብለው ከታዩ ሌላ ነገር ለመጠርጠር የምንፈጥን ከሆነማ በጣም ችግር ይፈጠራል። ምሳሌ ሊሆኑ የሚችሉ ብዙ ነገሮችን አንባቢያን ራሱ ቢያስቧቸው አመክንዮው ምን ያህል ፉርሽ እንደሆነ መረዳት ይችላሉ። አንድ ጥሩ የካራቴ ተማሪ በዛ ቢባል ያናደደውን ሰው በቦክስ ሊዘርር ይችል ይሆናል እንጂ መንግሥት አይገለብጥበትም። ደግሞም መንግሥት በሥርዓቱ እውቅና ሰጥቶ ግብር የሚሰበስብባቸውን የካራቴ ትምህርት ቤቶች በዚህ ዓይነት አሉባልታ ሥማቸውን ማጥፋት ተገቢ አይደለም። ሰዎቹ እንደተባለው ‹‹መንግሥት ለመገልበጥ››ከሆነ እየተማሩ ያሉት ፈቃድ የሰጣቸው አካል ራሱ በሕግ ተጠያቂ ከመሆን አያመልጥም።
አዎን! አስተማሪያችን ነቢዩ ሙሐመድ
‹‹ጎረቤቱ ተንኮሉን የማያምነው ሰው በእርግጥም አላመነም››ብለውናልና ለጎረቤቶቻችን እንኳ የሥጋት ምንጭ መሆን አንፈልግም። አገራችን ለሁላችንም በቂ ናት! የሚያሻንም የጋራ ሕልም እንጂ ዘወትር በመካከላችን ተቀብሮ ሰላም የሚነሣ የጥላቻ ሰንኮፍ አይደለም! ክፍፍል ይብቃን።
አላህ ኢትዮጵያን ይባርክ!




